Рет қаралды 3,839
የቤተ እስራኤል ግዛት ታሪክ
የቤተ እስራኤል ግዛት በአሁኗ ኢትዮጵያ በሰሜን ምዕራብ ይገኝ የነበረ የአይሁድ ግዛት ነበር። በአፍሪካ ቀንድ ግዛቱ እንደነበረ ለመጀመርያ ጊዜ የተገለጸው በ12ተኛው ክፍለ ዘመን በቱዴላው ቤንጃሚን ነበር።
በቀደሙ የኢትዮጵያ አይሁዶች መሰረት ግዛቱ የተመሰረተው በ4ተኛው ክፍለ ዘመን በንጉስ ኢዛና ጊዜ አክሱም የክርስትያን ግዛት ከሆነች በኋላ ነበር።
በዘመናዊ ቤተ እስራኤላውያን መሰረት የአባቶቻቸው ምድር የጌድዮን ግዛት ይባል ነበር፤ የግዛቱ ስም የወጣው ግዛቱን መርቶታል ከተባለው የአይሁድ ነገስታት ሥርወ መንግስት አንፃር ነው። በ9ነኛው ክፍለዘመን የነበረኤልዳድ ሀ ዳኒ የተባለ አይሁዳዊ ተጓዥ ከ12ቱ ነገደ እስራኤል መካከል የሆነው የዳን ነገድ ራሱን የቻለ ግዛት እንደመሰረተ ተናግሮ ነበር። ከ15ተኛው ክፍለ ዘመን እስከ 17ተኛው ክፍለ ዘመን መጀመርያ በነበረው ጊዜ ውስጥ የአቢሲንያ ግዛት የቤተ እስራኤልን ግዛት ፈላሻ ብላ ትጠራው ነበር። በ16ተኛውና በ17ተኛው ክፍለ ዘመን ደግሞ አቢሲንያ ግዛቱን የሰሜን ግዛት ብላ ትጠራው ነበር፤ የዚህም ምክንያቱ ደምቢያ እና ወገራ ካጣ በኋላ በያዘው ቦታ ምክንያት ነው።
ግዛታቸውም እስራኤላዊ ማንነት ያለው፤ የብሉይ ኪዳን ሐይማኖትና ባህል ያላቸው በኢትዮጵያ ባህል ውስጥ ገብተው የተስፋፉ ከቀደመውም ጊዜ ጀምሮ ሕዝባቸው የይሑዲ እምነት እና የክርስትና እምነትን የሚከተል ነበር።
የአክሱም ግዛት የክርስትና ሐይማኖትን መቀበል የጀመረችው በኢዛና ዘመን ፍሬምናጦስና ኤደሲየስ የተባሉ ሁለት ሶርያዊ ወንድማማቾች ወደ ግዛቱ በመጡ ጊዜ ነበር። ይህ የሐይማኖት መቀየርም የዕብራዊነትን ባህሪ ይዞ የመጣው በከፊል ነበር፤ ይህም በፍርድ ቤት የተገደበና ከአክሱም ከተማ እስክ አዱሊስ ያለው የንግድ መስመር ላይ ብቻ ተፅዕኖ የፈጠረ ነበር።
በኢትዮጵያውያን መሰረት የቤተ እስራኤል ወርቃማው ዘመን ከ858-1270 ያለው ጊዜ ነበር። በ16ተኛው ክፍለ ዘመን ዳዊት ቤን ሰሎሞን ኢብን አቢ ዚምራ የተባለ ሰው የቤተ እስራኤልን አይሁዳዊነት ተቀብሎ ነበር፤ ነገር ግን ታልሙድን ፈጽሞ እንደማያውቁት ያውቅ ነበር።
በ1270 የክርስትያን ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት ተነሳ፤ ራሳቸውን የቻሉ የከፍታ ቦታዎችንም በማስገበር ሥልጣኑን ማጠንከር ፈለገ። ከ1314-1344 የመራው አምደ ፅዮንም ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ ሐይማኖታዊና ፖለቲካዊ ሕብረት የመፍጠር አላማ ተግባር ላይ ዋለ፤ ከዚያም ወዲህ ተከታታይ መሪዎች ብዙ የአይሁድ ማኅበረሰብ በሚገኝበት በሰሜን ምዕራብ በሚገኙት በሰሜን፣ ወገራ፣ ጽልመት፣ ጸገዴ እና ደምቢያ ዘመቻዎችን አካሄዱ።
ከ1414-1429 የመራው አፄ ይሥሐቅ ከቤተ እስራኤል መካከል የሚተባበሩት ነበሩት፤ እርሱም በአይሁድ መሪዎች የሚመሩትን ሰሜን እና ደምቢያን አሸነፈ። ጉልትም ታማኝነትን ለማረጋገጥና ለአጋዥነት እንደ ሽልማት ይሰጥ ነበር፤ ይሥሐቅም የጉልት ምድርን ለተባባሪዎቹ ሰጣቸው። ባለ ጉልቶችም ገበሬዎችን ያስገብሩ ነበር፤ ይህም በኢትዮጵያ ውስጥ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የንብረት አያያዝ ሥርዓት ነው። ይሥሐቅም በርስት አወራረስ ዙርያ አንድ አዲስ ህግ አመጣ፤ ይህም ርስቱን የሚወርሰው ክርስትያን የሆነ ሰው ብቻ እንዲሆን የሚል ነው፤ ስለዚህም ከፊሉ የአይሁድ ማኅበረሰብ መሬቱን አጣ። ይሥሐቅም እንዲህ አለ፦ "በክርስትና ሐይማኖት የተጠመቀ ሰው የአባቱን መሬት ይወርሳል፤ ከዚህ ውጭ የሆነ ግን ፈላሻ ይሁን" አለ። ፈላሻ ማለት መሬት አልባ ሰው ማለት ነው።
ከ1529-1543 የአዳል ሱልጣኔት ከኦቶማን ከመጡላቸው ሠራዊት ጋር በመሆን የአቢሲንያ ግዛትን ወረረች። የቤተ እስራኤል መሪዎችም በጦርነቱ ወቅት አቅጣጫቸውን በመቀየር የሙስሊም አዳል ሱልጣኔትን መደገፍ ጀመሩ። የአዳል ሠራዊት ግን ከእነሱ ጋር መተባበር ጥቅሙ አልታያቸውም፤ ስለዚህም ከአይሁዶች ጋር መዋጋት፣ አካባቢዎቻቸውን መያዝ፣ ኢኮኖሚያቸውን ማውደምና ብዙዎቻቸውን መግደል ጀመሩ። ይህም በመሆኑ የቤተ እስራኤል መሪዎች መልሰው የአቢሲንያና የፖርቹጋል ተባባሪ ሆኑ። የአቢሲንያ ግዛትም የተያዘባትን ግዛት ካስመለሰች በኋላ የሰሜን ግዛት ላይ ጦርነት አወጀች፤ የዚህም ምክንያቱ የአይሁድ መሪዎች በኢትዮ-አዳል ጦርነት ወቅት አቅጣጫቸውን ቀይረው ነበርና። በኢየሱሳውያን በሚመሩት በፖርቹጋል ሠራዊት ትብብር የአቢሲንያ ግዛት በአፄ ገላውዴዎስ ዘመን ቤተ እስራኤልን በመውረር አይሁዱን ንጉስ ሒራምን ገደሉት። በዚህም ጦርነት ምክንያት የያዙት አካባቢ አንሶ የሰሜን ተራሮችን ብቻ ያዘ።
በ16ተኛው ክፍለዘመን የግብፁ ዋና ረቢ የነበረው ረቢ ዳዊት ቤን ሰሎሞን ኢብን አቢ ዚምራ ሀላካ በተባለው በአይሁድ ህግ መሰረት በኢትዮጵያ የሚገኙት አይሁዶች በእርግጥም አይሁዶች እንደሆኑ መሰከረ።
ንጉስ ሒራም ከተገደለ በኋላ ንጉስ ራዲ የቤተ እስራኤል ግዛት መሪ ሆነ። ንጉስ ራዲም በአፄ ሚናስ ዘመን በተደጋጋሚ በአቢሲንያ ግዛት ላይ አመፀ።
በአፄ ሠርጸ ድንግል ዘመን አይሁዶች አመጹ፤ ንጉሰ ነገስቱም ከኦቶማን የተማረኩት መድፎች አደገኛ በሆነ ሁኔታ አፈነዳባቸው። በተራራ ምሽግ ሳሉ የተከበቡት አብዛኛዎቹ አይሁዶችም ራሳቸውን አጠፉ።
በቤተ እስራኤላውያን መሰረት ብዙ ነገስታት ነበራቸው። እነዚህም፦
- ፊንሀስ: በአክሱሙ ንጉስ ኢዛና ጊዜ የቤተ እስራኤል መሪ ነበር።
- ጌድዮን አራተኛ: የንግስት ዮዲት(በተለምዶ ጉዲት) አባት ነበር።
- ንግስት ዮዲት(በተለምዶ ጉዲት): ከ960 እስከ 1000 ድረስ ለ40 ዓመታት የመራች ሲሆን እርሷም የአክሱም ግዛትን ያፈረሰች ነበረች።
- ጌድዮን አምስተኛ: 1434-1468 የነበረ ሲሆን እርሱም በአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ላይ አመፅ ያስነሳ ነበር።
- ሒራም: በአፄ ገላውዴዎስ ጊዜ የቤተ እስራኤል መሪ ነበር።
- ንጉስ ራዲ: በአፄ ሚናስ ዘመን ከንጉስ ሒራም በኋላ የቤተ እስራኤል ንጉስ ነበር።
- ንጉስ ካሌብ: ከንጉስ ራዲ በኋላ በአፄ ሠርፀ ድንግል ጊዜ የቤተ እስራኤል ንጉስ ነበር።
- ንጉስ ጎሸን: በአፄ ሠርፀ ድንግል ጊዜ የቤተ እስራኤል ንጉስ ነበር።
- ንጉስ ጌድዮን ስድስተኛ: በአፄ ሱስንዮስ ጊዜ የቤተ እስራኤል ንጉስ ነበር፤ ሚስቱም ዮዲት ትባል ነበር።
- ንጉስ ፊንሀስ: ከጌድዮን ስድስተኛ በኋላ የነበረ የቤተ እስራኤል ንጉስ ነበር።
- ንጉስ ጌድዮን ሰባተኛ: የመጨረሻው የቤተ እስራኤል ንጉስ ሲሆን እርሱም በ19ነኛው ክፍለ ዘመን መጀመርያ ለኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ተሸነፈ።
ማጣቀሻ(Reference)
en.wikipedia.org/wiki/Kingdom...
Telegram: t.me/Historybkind
Tiktok: tiktok.com/@tarikhistory
#ethiopia #history #ኢትዮጵያ #ታሪክ #sultanate #ethiopianhistory #ethiopianorthodox #religion #christianity #judaism #beteisrael #israel #israelites #israël